መጽሐፈ መሣፍንት. Chapter 20
1 ፤ የእስራኤልም ልጆች ሁሉ ወጡ፥ ማኅበሩም ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ድረስ፥ ከገለዓድም አገር ሰዎች ጋር፥ ወደ እግዚአብሔር ወደ ምጽጳ እንደ አንድ ሰው ሆነው ተሰበሰቡ።
2 ፤ ከእስራኤልም ነገድ ሁሉ የሆኑ የሕዝብ ሁሉ አለቆች ሰይፍ በሚመዝዙ በቍጥርም አራት መቶ ሺህ እግረኞች በሆኑ በእግዚአብሔር ሕዝብ ጉባኤ ቆሙ።
3 ፤ የብንያምም ልጆች የእስራኤል ልጆች ወደ ምጽጳ እንደ ወጡ ሰሙ። የእስራኤልም ልጆች። ይህ ክፉ ነገር እንደምን እንደ ተደረገ ንገሩን አሉ።
4 ፤ የተገደለችውም ሴት ባል ሌዋዊው እንዲህ ብሎ መለሰላቸው። እኔና ቁባቴ በዚያ ለማደር ወደ ብንያም አገር ወደ ጊብዓ መጣን።
5 ፤ የጊብዓም ሰዎች ተነሡብኝ፥ ቤቱንም በሌሊት በእኛ ላይ ከበቡት፤ ሊገድሉኝም ወደዱ፥ በቁባቴም አጥብቀው አመነዘሩባት፥ እርስዋም ሞተች።
6 ፤ እኔም ቁባቴን ይዤ ቈራረኋጥጥኋት በእስራኤልም ዘንድ እንደዚህ ያለ ኃጢአትና ስንፍና ስለ ተሠራ ወደ እስራኤል ርስት አገር ሁሉ ሰደድሁ።
7 ፤ እነሆ፥ የእስራኤል ልጆች ሆይ፥ ሁላችሁ፥ ምክራችሁንና እዝናታችሁን በዚህ ስጡ።
8 ፤ ሕዝቡም ሁሉ እንደ አንድ ሰው ተነሥተው አሉ። ከእኛ ዘንድ ማንም ወደ ድንኳኑ አይሄድም፥ ወደ ቤቱም አይመለስም።
9 ፤ ነገር ግን በጊብዓ ላይ የምናደርገው ነገር ይህ ነው፤ በዕጣ እንወጣባታለን።
10 ፤ ወደ ብንያም ጊብዓ በመጡ ጊዜ እርስዋ በእስራኤል ላይ እንዳደረገችው እንደ ስንፍናዋ እንዲያደርጉ፥ ለሕዝብ ስንቅ የሚይዙ ከእስራኤል ነገድ ሁሉ ከመቶው አሥር ሰው ከሺሁም መቶ ሰው ከአሥሩም ሺህ አንድ ሺህ ሰው እንወስዳለን።
11 ፤ የእስራኤልም ሰዎች ሁሉ እንደ አንድ ሰው ሆነው በከተማይቱ ላይ ተሰበሰቡ።